ትዳርና የቤተሰብ ኑሮ

 

ለኦርቶዶክስ ጋብቻ መመሪያ

(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሰባት ስብከቶች ስለ ወንድ እና ሴት፡የትዳር ሕይወትና የትዳር ላይ ጥቃት)

6.  በእኛ ዘመን ያለው አንድምታ


የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርቶች ወንድና ሴት በመንፈሳዊ እይታ እኩል እንደሆኑና ትዳር ማለት የመሥዋዕትነት ፍቅር እንደሆነ በግልጽ ያሳያሉ፡፡ ነገር ግን እንደተገለጸው በኦርቶዶክስ አማኞች ዘንድ የዚህ ትምህርት አረዳድ በታሪካዊ፣ ማኅበራዊ፡ ባህላዊና ግላዊ ምክንያተቶች የተዛባ ሆኖ ቆቷል፡፡ እነዚህ በአጽንኦት የተሰጡ ሐዋርያዊ ትምህርቶች ይህንን የተዛባና የተሳሳተ አረዳድ ለማስተካከልና ሌሎች ማኅበራዊና ባህላዊ የሆኑ ጎጂ ጠባያትን ለማረም ሊረዱ ይችላሉ፡፡[1]

በስብከቶቹ ላይ እንደተገለጸው በኦርቶዶክስ አስተምህሮ ወንድና ሴት በተመሳሳይ ክብርና አምሳል የተፈጠሩና ከመጀመርያውም አንድ የነበሩ ናቸው፡፡ ይሄ አንድነትም በኦርቶዶክሳዊ ጋብቻ መልሶ ተገኝቷል፡፡ በባለትዳሮቹ መካከል ስምምነት እንዲኖር ያኽል የሥልጣን ተዋረድ መኖር አንዳለበት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ያሳስባል፡፡ ባል እንደ ራስ ሚስት ደግሞ እንደአካል እንዲያገለግሉ አድርጎ መግለጹም እርስ በእርስ መደጋገፍ አንዳለባቸው፤ አንዳቸው አንዳቸውንም እንዳይጠሉና እንዳይጎዱ አጽንኦት ለመስጠት ካለው ፍላጎት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አስተምህሮ ወንድ በመለኮታዊው አሠራር የበላይ ተደርጓል የሚለውን የተሳሳተ አረዳድ ለማስወገድና የሴቶችን ክብር ለማስጠበቅ ይረዳል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የትዳር ሕይወት ላይ ላለ አብዛኛውን ሓላፊነት ለሴቶች ለሚያሸክም ጾታ ተኮር የሓላፊነት ክፍፍል መልስ ሊሆን ይችላል ምክንያቱም ባልና ሚስት አንድ አካል በመሆናቸው የሕይወት ሸክማቸውን በጋራ ሊሸከሙት አንደሚገባ ያስተምራልና ነው፡፡

ከዚህም ባለፈ ሚስቶቻቸው ላይ ኃይልና ጉልበትን የሚጠቀሙ ባሎችን በግልጽ ይገስጻል፡፡ ባል የገዛ ሰውነቱን (ሚስቱን) የሚጠላ ከሆነ አብሮ ጠፊ እንደሆነ ገልጧል፡፡ ባሎች ከሚስቶቻቸው አክብሮትን ለማግኘት ቀጣይነት ያለው መልካም የሆነና አሳቢነት ያልተለየው ፍቅር መለገስ አለባቸው ይላል፡፡ በዚህም ጥሩ ስምምነት ያለበትና በሁለቱም በኩል አስደሳች የሆነ ግንኙነት ይኖራቸዋል ይላል፡፡ ይህ ትምህርት ኦርቶዶክሳዊ ባልነት ማለት መንፈሳዊ መሪነትና ራስን አሳልፎ መስጠት ማለት አንደሆነ በማስረዳት የሴቶችን ጥቃት ለማስቆም ይረዳል፡፡ በሌላ በኩል በትዳር ውስጥ ስለሚኖር ተራክቦ ባስረዳበት ትምህርቱ በሁለቱም ፈቃድና ፍላጎት መሆን እንዳለበት አጽንኦት መስጠቱ እንደ ትዳር ውስጥ እንዳለ አስገድዶ መድፈር (ባል ያለሚስት ፍላጎት በጉልበት ቢገናኛት)፣ ከመጠን ያለፈ የተራክቦ ፍላጎት፣ ወይም ሌሎች የፍትወት ስሜት ማርኪያ መንገዶች የባለትዳሮቹን ሰሜት፣ ክብርና ጤንነት በተጨማሪም የትዳሩን ጤንነት ሊጎዱት ስለሚችሉ ነው፡፡

በመጨረሻም ከገጠሙት ተሞክሮዎች በመነሣት በትዳር ሕይወት ስለሚፈጠር ችግር በጥልቀት ሲመክር በትዳር ውስጥ መቻቻል መኖር እንዳለበት ነገር ግን ትዳሩ በሁለቱ መካከል ጠላትነትን እየጨመረ የሚሄድ ከሆነ ሴቷ ከክፉ ባሏ ጋር ቤተሰቧ አንዳይበተን ብቻ ስትል አብራው መኖሯ በምንም መልክ ተቀባይነት የለውም፡፡ የዚህም ምክንያት የእርሷም ፣ የባሏም የልጆቻቸውም መንፈሳዊ ዕድገት በዚህ ትዳር ውስጥ በመገደቡ እንደሆነ ይገልጻል፡፡ ይሄ በተለይ ለቤተሰባቸው ወይም ለትዳራቸው ቅድሚያ በመስጠት ጎጂ የሆኑ የትዳር ጥቃቶችን ለሚያስተናግዱ ኦርቶዶክሳዊ ሴቶች ወሳኝ መልእክት ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሴቶች ከእንዲህ ዓይነት ትዳር ተለይተው ለብቻቸው ሳያገቡ መኖርን መምከሩ ለአንዳንድ ሴቶች መልካም ተግባራዊ አማራጭ ሊሆን ይችላል ምክንያቱም የሴቶች ይሄንን እርምጃ መውሰድ ባሎችን ክፉ ጠባያቸውን አርመው ትዳራቸውን ለማስተካከልና ወደቀደመ ሕይወታቸው ለመመለስ እንዲያስቡ ሊያደርጋቸው ይችላል፡፡ በእርግጥ ፍቺውን ከሴትነቷ ጋር የተያያዙና ንብረት ነክ የሆኑ ጉዳዮች ሊያጓትቱት ይችሉ ይሆናል፡፡ በእንዲህ ዓይነት ጊዜ አንድ ዓይነት መላ ወይም መንገድ ብቻ ላይኖር ይችላል፡፡ ምንም ስንኳ ውሳኔው የሴቷ ቢሆንም የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ምክሮች የውሳኔ ዕድሎቿን ለማስፋት ይረዳሉ፡፡

ሦስት ሁኔታዎች ግን መታወቅ አለባቸው፡- 1) ኦርቶዶክሳዊ የሆነ ሁሉ በቤተክርስቲያን ትምህርት ይታነጻል ማለት እንዳልሆነ ምክያቱም ሁሉም ተመሳሳይ መንፈሳዊ ዕውቀትና አረዳድ ስለማይኖረው

2)  እነዚህ ትምህርቶች የኃይለኛነት ጸባይን ሊፈጥሩ የሚችሉ ከአካላዊ ዕድገት፣ ከሥነ ልቡና እና ከአካባቢያዊ ተጽእኖ የሚመጡ ምክንያቶችን በተመለከተ የተሟላ አስተያየት መስጠት ስለማይችሉ፤ በሥነ-ልቦና ሕክምና መታገዝ እንደሚችሉ ማወቅ[2]
3) አንዳንድ መምህራን ስለ ኦርቶዶክሳዊ ጋብቻ፣ ስለ የትዳር ጥቃትና ለሕፃናት ስለሚሰጥ መንፈሳዊ ምክር በቂ ዕውቀት ስለማይኖራቸው እነዚህን ትምህርቶች ለምእመናኑ በተገቢው ሁኔታ ማድረስ ላይ ችግር ሊያጋጥም ስለሚችል የመምህራኑንም ዕውቀትና አረዳድ ማማከል ያስፈልጋል[3]፡፡


[1] የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትርጓሜዎች (ትምህርቶች) ጸባይንና የተሳሳቱ አረዳዶችን ለመቀየር ያላቸውን አቅም Gassin, “Eastern Orthodox Christianity,” 2015 ይመልከቱ፡፡

 

[2] James Gilligan, Violence: Reflections on our Deadliest Epidemic (London: Jessica Kingsley Publishers, 1999); Donald Dutton, The Abusive Personality: Violence and Control in Intimate Relationships (New York: Guilford Publications, 2007); Linda Mills, “Shame and Intimate Abuse: The Critical Missing Link between Cause and Cure,”Children and Youth Services Review 30 (2008): 631–63.

 

[3] በኦርቶዶክስ ትውፊት አማኞች ኃጢአታቸውን የሚናዝዛቸው የንስሓ አባት በነፍስ ወከፍ ይኖራቸዋል፡፡ የንስሓ አባት በጥንዶች ሕይወት ውስጥም በጥልቀት ተሳታፊ ሲሆን ችግሮች በሚኖሩበትም ጊዜ ጥንዶቹ ቀድመው የሚያሳውቁት ለእርሱ ነው፡፡






ምዕራፍ 5 ወደ ይዘቶች ተመለስ ምዕራፍ 7